Friday, December 6, 2013

“ታህሳስ 5 ከሰአት በኋላ ለመገደል ፈርሜአለሁ”

SOURCE: GOLGUL

(ዶ/ር ካሳሁን በጋሻው)euthanasia

ታህሳስ 5 ከሰአት በኋላ ለመገደል ፈርሜአለሁ ገጽ 410 ይላል የስደተኛው ማስታወሻ፤ አቶ ተስፋዬ ገብረአብ “ጓደኛዬ” የሚለው ሆላንዳዊ ስለያዘው የሞት ቀጠሮ ሲያብራራ፤-
ለሚቀጥለው … ማስታዉሻ መጽሀፉ ይረዳው ዘንድ ሆላንድ ውስጥ የሞት ቀጠሮ እንዴት እንደሚያዝ ከዚህ በታች አብራራለሁ፤ ከዚያ በፊት ግን ስለ ስደተኛው ማስታወሻ የምለው ከዚህ የሚከተለውን ነው፤ ጫልቱ ብሎ የሰየማትን ተዋናይ እዛው የቡርቃ ዝማታው ላይ ቢከታት ኖር ገጸ ባህርይዋ ከዛ ጋር ይሰምርለት ነበር፡፡ ነገር ግን ከአለቆቹ የደረሰው ትእዛዝ አማራና ኦሮሞን ማፋጀት የኢትዮጵያን ስማ ማጥፋት በመሆኑ የግድ መካተት ነበረባት፤ በጎሳ እምነት የተለከፉ ሰዎች አመለካከታቸው ወደሌላ ሰውነት እንደተሰራጨ ካንሰር ነው፤ ቢነግሩአቸው ቢያስረዷቸው አይጠሩም፤ የተስፋዬ ገብረአብ ተማሪዎች በቀደም ሳውዲ አረቢያን ተቃውሞ ሰልፍ ላይ በእንግሊዝኛ  “እኛ ኢትዮጵያዊ አይደለንም ሳውድ አረቢያ ሴቶቻችንን መድፈር አቁሚ፤ ወንዶቹን መግረፍ አቁሚ” እያሉ መፈክር ይዘው ሳይ ምን ያህል እንደዘቀጥን እነ ተስፋዬም የደከሙበት ፍሬ ማፍራቱን ሳይ አዘንኩ፤ ምን ለማለት ፈልገው እንደሆነም ግልጽ አይደለም “ኢትዮጵያውያንን አሰቃዩ እኛን ደርባቹህ የምታሰቃዩን ኢትዮጵያዊ መስለናችሁ ነው ለማለት ነው?” ማንስ ቢሆን ለምን ይሰቃያል? ተስፋዬና አለቆቹ ግዜው ሲደርስ በዘር ማጥፋት ወንጀል ለፍርድ ሊቀርቡ የሚገባቸው ሰዎች ናቸው፤
ወደ ተነሳሁበት ልመለስና ለመግደል የሚፈረመው እንዴት ነው? ተስፋዬና አለቆቹ የሚቃወማቸውን ሁሉ ያለተከላካይ ስለሚያጠፉ የሰው ሕይወት ዋጋ ግንዛቤውም ስለሌላቸው ሌላውም አገር እንዲሁ ይመስላቸዋል፤ “ዐይን አላቸው አያዩም ጆሮ አላቸው አይሰሙም”
በሕክምና በሕጋዊ መንገድ መሞት፤
ይህ ድርጊት በአብዛኛው አገሮች እንደ ወንጀል የሚታይ ሆላንድ ውስጥ ግን በሕጋዊ መንገድ የሚካሄድ አሰራር ነው፤ በጣም ከባድና አነጋጋሪም ነው፤ እኛ ማነንና ነው የሰው ሕይወት የምናጠፋው ወይም ለመሞት ፈቃድ የምንሰጠው? በሽተኛው መረዳት ካልተቻለና ብዙ የሚሰቃይ ከሆነ ከስቃዩ ማላቀቅ ወንጀል ነው ወይ? እራሱን የቻለ ከሁለት ክፉ ምርጫዎች (dilemma) አንዱን መቀበል ነው። ይህ የሕክምናስ ስነምግባር (medical ethics) ነው ወይ? ሐኪም ሊያድን እንጂ ሊገል ነው ወይ የተማረው የመሳሰሉት እርስ በርስ የሚቃረኑ ሀሳቦች ጉዳዩን ያወሳስቡታል፡፡
ተስፋዬ ገብረአብ ሆን ተብሎ ጎሳዎችን ለማጋጨት በታቀደ አሰራር ውስጥ ለፖለቲካ ግብ እንዲመች እራሱን የቻለ ቅደም ተከተል ያለው ኢትዮጵያን ለማፍረስ አንድነትን ለማናጋት በሚከናወን አጀንዳ ስር ነው የተለያዩ ፍሬ ከርስኪ አጀንዳዎቹን የሚያቀርብልን። ከዚያ መሃል ግን ሃላፊነት በጎደለው መልኩ ያላየውን አየሁ ያልሰማውን ሰማሁ ብሎ ይተርካል፡፡
እኔ የዚህ ጽሁፍ ጸሐፊ የሞት ቀጠሮ ተብሎ የሰፈረው ታሪክ እንደ መጽሀፉ አብዛኛው ክፍል በጫት ምርቃና ላይ ተመርኩዞ የተደረገ እንጂ እሱ ባለው መሰረት አለመሆኑን ከዚህ በታች አስረዳለሁ፡፡
በእንደዚህ አይነት መንገድ በሐኪም እርዳት ለመሞት የፈለገ በሽተኛ በቅድሚያ በሕክምና መዳን የማይችል በሽታ እንደያዘው መረጋገጥ አለበት፤ እነዚህ በሽተኞች አብዛኞቹ የካንሰር በሽተኞች ሲሆኑ የተያዙበት ካንሰር ወደ ተለያዩ የሰውነት ክፍሎች በመሰራጨቱ ምክንያት በቀዶ ጥገና “በኪሞ ቴራፒ” በጨረር ሕክምና ሊረዳ እንደማይችል የተረጋገጠ ነው።

  1. በዚህ ደረጃ ላይ የሚገኙ በሽተኞች ከፍተኛ የሕመመ ማስታገሻ “ሞርፊን” እያገኙ ሕመሙን ማስታገስ ይከብዳል፤ ምግብ መመገብ አቁመዋል፤ የሚወስዱት ፈሳሽ በጣም አነስተኛ ነው፤ ስለማይመገቡም ሰውነታቸው አልቆ አጽማቸው ነው የቀረው፤ ስዕላዊ ግንዛቤ እንዲኖራቸሁ በድርቅ ግዜ የሚታየው አይነት ክሳት አብዛኞቹ ላይ ይታያል፤
  2. ምንም እርምጃ ባይወሰድ እነዚህ በሽተኞች በሳምንት ግዜ ውስጥ በራሳቸው ይሞታሉ፤
ልብ አድርጉ እንግዴህ ለሞት ቀጠሮ የያዘው የተስፋዬ ገብረአብ ጓደኛ አትክልቱን ሲኮተኩት ነበር፤ ልክ አማራና ኦሮሞ እያለ ሃላፊነት የጎደለው መዘላበዱን እንደለመደው እዚህም የሚያጣራ አይኖርም በሚል ነጭ ውሸቱን ያስፋፋል፡፡
ወደ ዋናው አርእስት ልመለስና ሕይወቱ በሕክምና ባለሙያ እንዲጠናቀቅለት የሚፈልገው በሽተኛና ቤተሰቦቹ ለበሽተኛው ዶክተር ፍላጎታቸውን ያሳውቃሉ፡
  • ዶክተሩ በመጀመሪያ ደረጃ ጥያቄው ተገቢ መሆኑን ይመረምራል፤ በሽተኛው መዳን አይችልም ወይ? ማድረግ የሚገባን ያላደረግነው ነገር አለ ወይ? ስቃዩን ለመቀነስ የሚደረግለት እንክብካቤ በቂ ነው ወይ? ይከታተሉት የነበሩት ሰፔሻሊስቶች ማድረግ የሚችሉትን ሁሉ አድርገውለታል ወይ? ምንም ባናደርግስ ምን ያህል ግዜ በሕይወት ይቆያል? ለሚሉት ጥያቄዎች መልሱ ጥያቄው ተገቢ ነው የሚለው ድምዳሜ ላይ ከደረሰ፤ ጥያቄውን ለሌላ (independent) ነጻ የሆነ ዶክተር ያቀርባል፤
  • ይህ ነጻ ዶክተር ጋባዡን ዶክተር እና በሽተኛውን የማያውቅ ዶክተር ነው ይህም ስራውን ነጻ ሆኖ ያለአድልኦ እንዲፈርድ ይረዳዋል፤ የበሽተኛውን የሕክምና ዶኩመነቶች ያጠናል፤ እስካሁን መደረግ የሚገባው ሕክምና መደረጉን ያረጋግጣል፤ ያን ካደረገ በኋላ ወደ በሽተኛው በመሄድ የጥያቄውን ተገቢነት ያረጋግጣል፤ ጥያቄው ተገቢና ህግ የተከተለ ነው ብሎ ካመነ ማጠቃለያ ሪፖርት ጽፎ ጥያቄውን ላቀረበው ዶክተር ተቃውሞ እንደሌለው ያሳውቃል፤ መዘነጋት የሌለበት በሽተኛው ጥያቄውን በፈለገው ግዜ ማንሳት ይችላል፤
  • ዶክተሩ ከነጻ ዶክተሩ ሪፖርቱን ካገኘ በኋላ በአካባቢው ከሚገኘው ፋርማሲ ጋር በመመካከር ለዚሁ የሚረዳውን መድሃኒት ያዛል፤ መድሃኒቶቹም ሁለት ሲሆኑ የመጀመሪያው በሽተኛውን ጥልቅ እንቅልፍ ውስጥ ይከተዋል ከዛ በኋላ የሚደረገውን በሽተኛው አይሰማውም፤ ከተኛ በኋላ የልብና የሳምባ ስራውን የሚያስቆመው መድሃኒት ይወጋል በሽተኛውም ይሞታል ማለት ነው፤ የዶክተሩ ስራ ገና አልተጠናቀቀም፤ በሽተኛው መሞቱን ካረጋገጠ በኋላ ለተረኛ ፖሊስ ዶክተር ደውሎ ሕጋዊ በሆነ መንገድ የሰው ሕይወት ማጥፋቱን ጠቁሞ በህጋዊ መንገድ እንደተካሄደ መጥቶ እንዲመረምርለት ያሳውቃል ከዚያም ቤተሰብን እግዜር ያጽና ሙት ነፍስ ይማር ብሎ ይለያያል፤
  • የፖሊስ ዶክተሩ ሀኪሙ ትቶለት የሄደውን ሪፖርቶች ያነባል፤ ነጻ ዶክተሩ የሰጠውን ሪፖርት ያነባል፤ ለበሽተኛው ለመሞት የተሰጡትን መድሃኒት ብልቃጦችን ከመረመረ በኋላ ሬሳውን በቅጡ መርመሮ ቤተሰብን ካበረታታ በኋላ የራሱን ግምገማ ለፍርድ ሚኒስቴር ያቀርባል፤ ይህ በተካሄደ በስድስት ሳምንት ግዜ ውስጥ የመሞቻ መርፌውን ለወጋው ዶክተር ህጉን ተከትሎ መስራቱንና ከተጠያቂነት ነጻ የሚያደርገውን ወረቀት ከፍርድ ሚኒስቴር ያገኛል፤ ቅደም ተከተሉ ላይ ከሕግ ውጪ የተደረጉ ነገሮች ካሉ ደግሞ በሕግ ይጠየቃል ማለት ነው፤
ማጠቃለያ፦ የሰው ሕይወት በቀላሉ በቀጠሮና በፊርማ የሚያጠፉት የተስፋዬ አለቆች እንጂ አትክልቱን የሚኮተኩት ሕይወት ስለሰለቸው ብቻ የሚገደል ሰው የለም፤ አቶ ተስፋዬም አብረው ለዘመናት የኖሩትን ሕዝቦች እርስ በርስ ከማፋጀት የጽሁፍ ቸሎታውን ለማስማማት፤ ለማፋቀር ቢጠቀምበት የሰራውን ይህ ነው የማይባል ወንጀል ለማካካስ ይረዳው ይሆናል።

No comments:

Post a Comment